በሴቶች ላይ ወሲባዊ ጥቃቶችና ትንኮሳ በመፈጸም የተበየነበት ሀዱሽ ገብረ ሥላሴ ቅባቱ ከብሪታንያ ወደ ኢትዮጵያ ተባረረ
Description
በሴቶች ላይ ወሲባዊ ጥቃቶችና ትንኮሳ በመፈጸም የተፈረደበት ሀዱሽ ገብረ ሥላሴ ቅባቱ ዛሬ ወደ ኢትዮጲያ ተጠረዘ ፤ ብሪታንያ ተገን ጠያቂዎች ወደ ቀድሞ ወታደራዊ ጦር ሰፈሮች ልታዛውር ነው
የብሪታንያ መንግሥት በሴቶች ላይ ወሲባዊ ጥቃቶችና ትንኮሳ በመፈጸም የተፈረደበትን ሀዱሽ ገብረ ሥላሴ ቅባቱን ወደ ኢትዮጲያ መጠረዙን ዛሬ አስታወቀ።
የብሪታንያ የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት፣ በስህተት ከታሰረበት ከተለቀቀ ፣48 ሰዓታት ከሚጠጋ ጊዜ በኋላ እሁድ ዳግም የታሰረው ሀዱሽ ኢትዮጵያ መድረሱን ዛሬ አስታውቋል። በአንዲት የ14 ዓመት ልጃገረድና በአንዲት አዋቂ ሴት ላይ የወሲብ ጥቃትና ትንኮሳ በመፈጸም አንድ የብሪታንያ ፍርድ ቤት ባለፈው ወር የጥፋተኝነት ብይን ያሳለፈበት የ38 ዓመቱ ሀዱሽ ከተወሰነበት የአንድ ዓመት እሥራት ውስጥ አንድን ወር በእስር ቤት አሳልፎ ነበር።
በሌላ በኩል ብሪታንያ በሆቴሎች ውስጥ የምታኖራቸውን ተገን ጠያቂዎችን ወደ ቀድሞ ወታደራዊ ጦር ሰፈሮች ለማዛወር ማቀዷን አስታውቃለች። ሁለት አገልግሎት መስጠት ያቆሙ ጦር ሰፈሮች በጊዜያዊነት ቁጥራቸው 900 ለሚደርስ ወንድ ስደተኞች ማቆያ እንደያገለግሉ መታቀዱን የብሪታንያ ጠቅላይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ አስታውቀዋል።
ይሁንና አሁንለተገን ጠያቂዎች ማቆያ ለታሰቡት የቀድሞ የጦር ሰፈሮች ማደሻ ሆኖ ለሌሎች አገልግሎቶች የሚያስፈልገው ገንዘብ ለሆቴሎቹ ይወጣ ከነበረው የሚበልጥ መሆኑ ማነጋገሩ አልቀረም። መንግሥት ግን የሚያስወጣው ገንዘብ ቢበዛም የህዝብን ቅሬታ ለማቃለል እስከረዳ ድረስ አያሳስበኝም ብሏል።
ስለሀዱሽ ገብረሥላሴ ቅባቱ ወደ ኢትዮጵያ መጠረዝና፣ ብሪታንያ ተገን ጠያቂዎች ወደ ቀድሞ ጦር ሰፈሮች ልታዛውር ማቀዷን በተመለከተ የለንደኑን ወኪላችንን ድልነሳ ጌታነህን በስልክ አነጋግረነዋል።
ድልነሳ ጌታነህ
ኂሩት መለሰ
ሸዋዬ ለገሠ






















