በዓለም ቅርስነት የተመዘገበው «ጊፋታ»
Description
አቶ አብረሃም ባቾሬ ጉተራ የተባለው የዎላይታ የአገር ሽማግሌዎች መማክርት ጉባዔ አባል ናቸው። አቶ አብርሃም ከ18 ዓመት በፊት የጊፋታ በዓል ዕውቅና እንዲያገኛ በመገናኛ ብዙኀን ሲወተውቱ ከነበሩት ጥቂት የብሔር ተወላጆች መካከል ናቸው። አቶ አብረሃም ዛሬ የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባሕል ድርጅት (ዩኔስኮ)የወላይታ ብሔር የዘመን መለወጫ በዓል «ጊፋታ» በማይዳሰሱ የዓለም ቅርስነት መመዝገቡን ስሰማ ተኝቼ አደርኩ ይላሉ።
ምዝገባው የፈጠረው ሥሜት
የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባሕል ድርጅት (ዩኔስኮ) የወላይታ ብሔር የዘመን መለወጫ በዓል «ጊፋታ» በሰው ልጆች ወካይ ቅርስነት መመዝገቡን ያስታወቀው ትናንት ነው። ድርጅቱ ዕውቅናውን ያበሠረው በሕንድ ኒው ዴልሂ እየተካሄደ በሚገኘው 20ኛው የድርጅቱ የማይዳሰሱ የባሕል ቅርሶች ጥበቃ ኮሚቴ ጉባኤ ላይ ነው።
ባህሉ በዩኔስኮ መመዝገቡን ተከትሎ በወላይታ ዞን የተለያዩ ከተሞች ሕዝቡ ደስታውን በሠልፍ እየገለጸ ይገኛል።የወላይታ ሶዶ ከተማን ጨምሮ በዞኑ የተለያዩ ወረዳ ነዋሪዎች ጎዳና በመውጣት ደስታቸውን በባህላዊ ጭፈራ ገልጸዋል። እንዲሁም የተሽከርካሪ ጥሩምባዎችን በማስጮህ ድርጅቱ ያሳለፈው ውሳኔ ያስደሰታቸው እንደሆነ አሳይተዋል።
የጊፋታ ትሩፋቶች
መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ጊፋታ ማለት «መጀመሪያ» ማለት ሲሆን ከአሮጌ ወደ አዲስ፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን በማሸጋገር እንደ ድልድይ ይቆጠራል። በጊፋታ ወቅት፣ ወላይታዎች የብሔሩን ጭፈራ ይጨፍራሉ፣ በባህላዊ ምግቦች ይደሰታሉ። የጊፋታ ፋይዳ ያለፉትን ጉዳዮች ማስወገድ እና እንደገና መጀመር ነው፡፡ በተለይም ያለፉትን አለመግባባቶች ማስታረቅ እና የቤተሰብ እና የማኅበረሰብ ግንኙነቶችን ማጠናከር መሆኑንም የብሔሩ የአገር ሽማግሌዎች ይናገራሉ።
የጊፋታ መመዝገብ ምን ዓይነት ጥቅሞች ይኖሩታል ?
አቶ አዳነ አይዛ የባህልና የታሪክ ተመራማሪና ቅርሱን ለማስመዝገብ በተደራጀው ኮሚቴ ውስጥ በአባልነት አገልግለዋል። የወላይታ ብሔር የዘመን መለወጫ በዓል «ጊፋታ» በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባሕል ድርጅት (ዩኔስኮ) በቅርስነት ለማስመዝገብ በርካታ ውጣ ውረዶች እንደነበሩ አቶ አብራሃም ገልጸዋል።
ጊፋታ በማይዳሰሱ የዓለም ቅርስነት መመዝገቡ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው የጠቀሱት አቶ አብረሃም «ይህ ማለት በዓሉ አሁን ተጨማሪ የሚንከባከበው አካል አግኝቷል ማለት ነው መጀመሪያ የቅርሱ ባለቤትነት የዎላይታ ብሔር ነበር፣ ቀጥሎ የአገር ቅርስ ወደ መሆን ተሸጋገረ፡፡ አሁን በመጨረሻ ደግሞ የዓለም ሕዝበ ቅርስ ሆነ፡፡ ይህ ማለት ከእንግዲህ ዓለም አቀፍ ተቋም ጭምር የሚንከባከበው ሀብት ሆነ ማለት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በዓሉ የሕዝብ ትሥሥርን ለመፍጠር እንዲሁም ከቱሪዝም ሥራዎች በተያያዘ ዘርፈ ብዙ ጥቅም ይኖረዋል ተብሎ ይጠበቃል» ብለዋል።
በሸዋንግዛው ወጋየሁ
ሸዋዬ ለገሠ
አዜብ ታደሰ























