አሳሳቢው መደበኛ ያልሆነ ፍልሰት በኢትዮጵያ
Description
በኢትዮጵያ መደበኛ ያልሆነ ፍልሰት እና በሰዎች የመነገድ ወንጄል ሰፊ እና ውስብስብ ችግር መሆኑን በዘርፉ የሚሰሩ ዓለም አቀፍ እና ሀገር በቀል ተቋማት ይገልፃሉ። ይህ ችግርም አሳሳቢ እና ቀጣይነት ያለው ሆኖ በርካታ ሰዎችን በተለይም ወጣቶችን ሰለባ እያደረገ ነው።
ከዓመት በፊት የወጣ ገለልተኛ ዘገባ እንዳመከተው የአፍሪካ ቀንድ በተለይ ጅቡቲ ወደ ሳዑዲ አረቢያ ለሚሰደዱ ኢትዮጵያውያን ዋነኛ መሸጋገሪያ ሲሆን በአማካይ 12,000 ሰዎች በየወሩ ይጓዛሉ። በቅርቡ በጉዳዩ ላይ በኢትዮጵያ በተካሄደ ውይይት ላይ መደበኛ ባልሆነ መንገድ ከአገር የመውጣት ሂደት ዜጎችን ብቻ ሳይሆን በአገር ደህንነትና በፋይናንስ ስርአቱ ላይ የፈጠረው ስጋት እየጨመረ መምጣቱ ተገልጿል።
የአሜሪካ መንግስት በቅርቡ ያወጣው ዓመታዊ ህገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር ሪፖርት እንደሚያሳየው በኢትዮጵያ በአብዛኛው ህገወጥ የሰዎች ዝውውር ድንበር ተሻጋሪ ቢሆንም በሀገር ውስጥም ችግሩ ስር የሰደደ ነው።እንደ ሪፖርቱ በተለይም ሴቶች እና ልጃገረዶች በመካከለኛው ምስራቅ ለግዳጅ ስራ ወይም ለፆታዊ ብዝበዛ ሲጋለጡ ፤ ወንዶች ደግሞ በግዳጅ ስራዎች የጉልበት ብዝበዛ ይፈጸምባቸዋል። በአገር ውስጥ ሕጻናት በግዳጅ በልመና፣ በጎዳና ተዳዳሪነት ይበዘብዛሉ፣ ለትጥቅ ግጭትም ይመለመላሉ።
በጉዞ ላይ ለዕስር የሚዳረጉ፣ባህር አቋርጠው ለመሄድ ሲሞክሩ ህይወታቸው የሚያልፍም በርካቶች ናቸው።የዚህ ችግር ሰለባ በአብዛኛው የነገ ተስፋ የሚባሉት ወጣቶች መሆናቸው ደግሞ፤ ችግሩን አሳሳቢ ያደርገዋል።
በኢትዮጵያ እየጨመረ በመጣው መደበኛ ያልሆነ ፍልሰት ገፅታ ፣ ገፊ ምክንያቶች እና መፍትሄዎች የዛሬው የእንወያይ ዝግጅት ትኩረት ነው። በዚህ ውይይት አራት እንግዶችን ተሳትፈዋል።
1,ፕሮፌሰር ክንፈ አብርሃም-------የስነህዝብ ባለሙያ ናቸው። መደበኛ ባልሆነ ፍልሰት ላይ ጥናቶች አድርገዋል።ብዙ ፅፈዋል።
2,አቶ ዳንኤል መለሰ ------ንጋት ግሎባል ኢኒሽየቲቭ የሚባል ከፍልሰት ተመላሾችን የሚደግፍ ድርጅት- መሥራች እና ኃላፊ ናቸው።
3,አቶ እዩኤል ደምሴ -----ከዓለም አቀፉ የፍልሰት ድርጅት በኢትዮጵያ መደበኛ ያልሆነ ፍልሰት ጥበቃ ክፍል ሀላፊ
4,ሚሊዮን ሀይለስላሴ ---------የዶቼቬለ የመቀሌ ዘጋቢ ነው። በጉዳዩ ላይ በርካታ ዘገባዎችን ሰርቷል።
ሙሉ ዝግጅቱን የድምፅ ማዕቀፉን ተጭነው ያድምጡ።
ፀሐይ ጫኔ