የኢትዮጵያ መንግሥት ከህወሓት እና ከኤርትራ ሲወዛገብ እውነተኛ ንግግር እንዲደረግ ከትግራይ ጥሪ ቀረበ
Description
በትግራይ የሚንቀሳቀሱ ሲቪል ተቋማት ያለው ፖለቲካዊ ውጥረት የሚያረግብ እውነተኛ እና ሁሉ አካታች ውይይት እንዲጀመር ጥሪ አቀረቡ። ከዚህ በተጨማሪ ተቃዋሚው ሳልሳይ ወያነ ትግራይ በበኩሉ በአፍሪካ ቀንድ እየታየ ያለው የተካረረ ፖለቲካዊ ውጥረት ወደከፋ ሁኔታ እንዳያመራ ዓለማቀፍ ማሕበረሰብ ሚናው ይወጣ ብሏል።
በህወሓት እና የኢትዮጵያ መንግስት መካከል እንዲሁም በኤርትራ እና ኢትዮጵያ መንግስት መካከል እየታየ ያለው ውዝግብ ባየለበት በዚህ ወቅት ትላንት የሰላምና ውይይት መልእክት በማለት መግለጫ ያወጡት በትግራይ የሚንቀሳቀሱ ስምንት ሲቪል ማሕበራት እየታዩ ያሉ ፖለቲካዊ ችግሮች ወደከፋ ሁኔታ ሳይሻገሩ በውይይት እንዲፈቱ ጠይቀዋል።
በተለይም በትግራይ ያለው ፖለቲካዊ ክፍፍል አሳሳቢ ሆኖ እንዳለ ሲገልፁ የቆዩት እነዚህ ሲቪል ተቋማት፥ በሰላም እና አንድነት የተባሉ መድረኮች እየተካሄዱ መሆኑ ብንታዘብም ሁሉ አካታች አይደሉም ብለዋል።
የተለየ ፖለቲካዊ አመለካከት ያላቸው የፀጥታ እና ፖለቲካ ሐይሎች፣ ሲቪል ማሕበራት እንዲሁም የተለያዩ የማሕበረሰብ ክፍል የሚወክሉ አካላት ያሳተፈ እውነተኛ ንግግር እንዲደረግ ጥሪ እናቀርባለን ሲሉ እነዚህ ስምንት ሲቪል ተቋማት በጋራ መግለጫቸው አስታውቀዋል።
ቅድሚያ ለሰብአዊ መብቶች፣ በሴቶች ጉዳይ የሚሰሩ ጎርዞ እና ይኾኖ የተባሉ ተቋማት ጨምሮ ሌሎች በዚሁ መግለጫቸው ሁሉም አካላት ለሰላም እና ውይይት ዝግጁነታቸው ያሳዩ ብለዋል።
የዳግም ጦርነት ስጋት
ይህ በእንዲህ እንዳለ ሌላው በወቅታዊ ጉዳዮች ዙርያ መግለጫ ያወጣው በትግራይ በተቃዋሚነት የሚንቀሳቀሰው ሳልሳይ ወያነ ትግራይ በበኩሉ ትግራይን ከዛም አልፎ አፍሪካ ቀንድን መልሶ ወደ ግጭት ሊያስገባ የሚችል ሁኔታ መኖሩ በመግለፅ ለዚህ ትኩረት እንዲሰጥ አመልክቷል።
አቶ አሉላ ሃይሉ የትግራይ ህዝብ ካለፈው ጦርነት ጠባሳ አላገገመም ያሉ ሲሆን በሚልዮን የሚቆጠር ህዝብ ከጦርነቱ በኃላ ጭምር ወደ ቀዬው ሳይመለስ ባለበት ዳግም ግጭት እንዳይከሰት የበለጠ ጥንቃቄ ያሻል ብለዋል።
የዓለምአቀፉ ማሕበረሰብ ሚና
የሳልሳይ ወያነ ትግራይ ሊቀመንበር አሉላ ሃይሉ በህወሓት እና የኢትዮጵያ መንግስት መካከል የቆየ ልዩነት እንዲሁም መነሻው የተለያዩ ፍላጎቶች ያደረገ የኢትዮጵያ እና ኤርትራ መንግስት ፍጥጫ ወደለየለት ጦርነት የሚገባ ከሆነ የትግራይን ህዝብ ለከፋ ሁኔታ የሚዳርግ በመሆኑ አስቀድሞ የጥንቃቄ እርምጃዎች እንደሚያስፈልጉ ያነሳሉ።
ከዚህ በተጨማሪ ዓለምቀፉ ማሕበረሰብም የሚጠበቅበት ሐላፊነት ይወጣ ሲሉም አቶ አሉላ ሃይሉ ጨምረው ይገልፃሉ።
ሚሊዮን ኃይለሥላሴ
እሸቴ በቀለ