አማራ ክልል በፋኖ ኃይሎችና በመንግሥት ወታደሮች ውጊያው ቀጥሏል ተባለ
Description
ትናንትና ምሽትን ጨምሮ ሰሞኑን በፋኖ ኃይሎች እና በኢትዮጵያ መንግሥት ወታደሮች መካከል በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች ውጊያ መኖሩ ተገለጠ ። በውጊያው የፋኖ ኃይሎች ተጨማሪ ቦታዎችን መቆጣጠራቸውም ተገልጧል ። የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ከበደ ደሲሳ «ጽንፈኛ» ሲሉ የገለጡት ኃይል ትንኮሳ ከመፈጸም ውጪ በየቦታው የመዋጋት አቅም የለውም ብለዋል ።
የፋኖ ኃይሎች በሰሜን ወሎ ዞን
በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች ሰሞኑን በነበሩ ውጊያዎች የፋኖ ኃይሎች በርካታ አካባቢዎችን መቆጣጠራቸው ተገለጠ ። ደቡብ ጎንደ እና ሰሜን ወሎ መገናኛ ቦታ በሆነችው ጨጨኾ ነዋሪ የሆኑ አንድ የአካባቢው ነዋሪ፦ ጨጨኾ፣ ዘቢጥ፤ ገረገራ እና አፍላቂትን ጨምሮ ዙሪያውን የፋኖ ኃይሎች እንደያዙት ለዶይቸ ቬለ ተናግረዋል ።
የፋኖ ኃይሎች በሰሜን ወሎ ዞን ብቻ ስድስት ወረዳዎችን መቆጣጠራቸውን ደግሞ የጨጨኾ ክፍለ ጦር ዋና አዛዥ ሻለቃ ሚኪያስ ለዶይቸ ቬለ ተናግረዋል ። ትናንት የመንግስት ወታደሮች ራያ ቆቦ በሚባል ቦታ ተኩለሽን አልፎ ሙጃ እና ኩልመስክን ለመቆጣጠር ሙከራ ቢያደርጉም ብርቱ ጉዳት እንደደረሰባቸውም አክለዋል ። «ፋኖዎች ወደ ኋላ እንደማፈግፈግ አሉለት፥ ተስቦ ገዥ ቦታ ሲገባ የስበት ማእከልን በመጠቀም አንድ ሠራዊት እንኳን ይዞ አልወጣም» ብለዋል ።
የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች አገልግሎት ሚኒስትር
የመከላከያ ሠራዊት ቃል አቀባይ ብርጋዴር ጄኔራል ጌትነት አዳነ ስለ ሁኔታው እንዲነግሩን በእጅ ስልካቸው ደውለን ብናጠይቃቸውም ከመንግሥት ኮሙኒኬሽን በኩል ካልመጣ መልስ እንደማይሰጡ ዐሳውቀዋል ። የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ከበደ ደሲሳ «ጽንፈኛ» ሲሉ የገለጡት ኃይል ትንኮሳ ከመፈጸም ውጪ በየቦታው የመዋጋት አቅም የለውም ብለዋል ። የተለየ ዝርዝር የሚሰጡት ነገር እንደሌለ በመጥቀስም ቀጣዩን ለዶይቸ ቬለ ተናግረዋል ።
«የተለየ መረጃ አድርገን የምንነግረው የለም ለሚዲያ የሚሆን፥ ጽንፈኛው ቡድን በየቦታው ትንኮሳ ነው የሚፈጽመው እንጂ ቆሞ የመዋጋት አቅም አደረጃጀትም የለውም» ሲሉም አክለዋል ።
ሌላ የፋኖ ታጣቂ በበኩላቸው፦ በሰሞኑ ውጊያ ሣንቃ፣ ዘቢጥ እና ዲባላን የመሳሰሉ ቦታዎችን መቆጣጠራቸውን ገልጠዋል ። «በፋኖ ቁጥጥር የገቡ ብዙ ወረዳዎች፤ ብዙ ቀበሌዎች አሉ አሁን ሰሞኑን በተደረገው [ኦፕሬሽን]ማለት ነው ። ጨጨኾ፤ ሣንቃ፣ ዘቢጥ፣ ዲባላ እና እነዚህ የመሳሰሉ ቦታዎች ያለበት የእኛ ኃይል ነውም ብለዋል ።
ውጊያው በአሁኑ ወቅት
ሰሜን ወሎ ላስታ ብልብላ ነዋሪ የሆኑ ሌላ አንድ ነዋሪ ያሉበትን አካባቢ ለረዥም ጊዜ የፋኖ ኃይሎች እንደተቆጣጠሩ በመግለጥ በሰሞኑ ውጊያ በአካባቢያቸው እንዳልነበር ተናግረዋል ። «ያው አሁን ሰላምነው ለዚህ ሁለት ቀን ያህል» የሚል አስተያየት ሰጥተዋል ።
በዛሬው ዕለትም ሰሜን ወሎ ሣንቃ የሚባል ቦታ ትንሽ ከፍ ብሎ በቅሎ ማነቂያ በሚባል ቦታ ዛሬም ውጊያ እንደነበር ተገልጧል ። ክልል ወቅታዊ ሁኔታ ለመጠየቅ የክልሉ የኮሙኒኬሽን ኃላፊ ዶክተር መንገሻ ፈንታው ጋር በተደጋጋሚ በእጅ ስልካቸው ብንደውልም ጥሪያችን ምላሽ አላገኘም ። በፋኖ ታጣቂዎች ተያዙ ስለተባሉ ቦታዎችም ሆነ በሰሞነኛው ውጊያ ስለተከሰቱ ጉዳዮች ዶይቸ ቬለ ከገለልተኛ ወገን ማረጋገጫም ሆነ ማስተባበያ ማግኘት አልቻለም ።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ታምራት ዲንሳ