ኢህአፓ ገዢው ፓርቲ እያሳደረ ባለው ጫና ምክንያት በቀጣዩ ምርጫ ላይ የሚኖረውን ተሳትፎ እንደሚገመግም አስታወቀ
Description
ኢህአፓ ገዢው ፓርቲ እያሳደረ ባለው ጫና ምክንያት በቀጣዩ ምርጫ ላይ የሚኖረውን ተሳትፎ እንደሚገመግም አስታወቀ። የፓርቲው ዋና ጸሐፊ ወይዘሪት ሚስጥረስላሴ ታምራት ዛሬ ለዶቼ ቬለ በሰጡት አጭር ቃለምልልስ ፓርቲው ሊያካሂድ አቅዶ የነበረው ህዝባዊ ስብሰባ የገዢው ፓርቲ ባሳደረው ጫና ምክንያት ተስተጓጉሏል። ፓርቲው በይፋዊ የማህበራዊ መገናኛ ገጹ አስቀድሞ ባጋራው መረጃ «የዜጎችን የመሰብሰብ እና የመቃወም መብቶች ላይ የሚደረግ ቀጥተኛም ሆነ ተዘዋዋሪ የአገዛዙ ክልከላ ሰላማዊ ትግሉን ማስቆም በፍጹም አይችልም» ብሏል። ለሕዝብ መገልገያነት መዋል የሚገባቸው የመንግስት አዳራሾች በስርኣቱ ሙሉ ቁጥጥር ውስጥ
በመሆናቸው እና በአዳራሾቹ የመገልገል መብታችንን እንደ ሁሉም የኢትዮጵያ ሕዝብ መብቶች ሁሉ «ተነጥቀናል» ያለው ፓርቲው የግል አዳራሾችን ለማነጋገር መገደዱን አስታውቋል፡፡
ይህንኑ ተከትሎ ሆቴሎች፣ ሲኒማና ትያትር ቤቶች እንዲሁም የግል አዳራሾች ማነጋገሩን ያመለከተው የፓርቲው መግለጫ ተቋማቱ ሙሉ ፈቃደኛ ከሆኑ በኋላ ባልታወቀ ምክንያት እንደማያካረዩት እና ውል መያዝ እንደማይቻል እንደገለጹለትም በዚሁ መግለጫው አመልክቷል።
በህዝባዊ ስብሰባው በሀገሪቱ ውስጥ እየተካሄደ ያለውን እና ተጨባጩን እውነታ ከሕዝቡ የመስማት ዕቅድ ነበረን ያሉት ዋና ጸሐፊዋ በደረሰብን ክልከላ ይህ «ሳይሳካ ቀርቷል » ብለዋል።
ክልከላው በኢህአፓ ላይ ብቻ የተፈጸመ ሳይሆን በሁሉም ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ላይ እንደተፈጸመም ሊቆጠር ይገባልም ብለዋል።
ነገር ግን ያነጋገርናቸው ሆቴሎች፣ ሲኒማና ትያትር ቤቶች እንዲሁም የግል አዳራሾች በሙሉ በቅድሚያ ፈቃደኝነታቸውን ገልጸውልን ውል ለመዋዋል ጫፍ ላይ ስንደርስ በማናውቀው መንገድና ምክንያት ሊያከራዩን እንደማይችሉ ሲገልጹልን ቆይተዋል፡፡
ኢህአፓ ነገ ቅዳሜ ህዳር 27 ቀን 2018 ዓ/ም አዲስ አበባ ሜክሲኮ አካባቢ በሚገኘው ዲ አፍሪክ ሆቴል አዳራሽ ህዝባዊ ስብሰባ ለማካሄድ ዕቅድ ጥሪ አድርጎ እንደነበር በመግለጫው አመልክቷል።
ታምራት ዲንሳ
ፀሐይ ጫኔ























