ትግራይ ክልልን ጨምሮ በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች የሚሰሩ ስምንት ሲቪል ማሕበራት ስጋትና ጥሪ
Description
በኢትዮጵያ መንግስት እና ህወሓት መካከል አለ የሚባለው አለመተማመን ሌላ ዙር ጦርነት እንዳያስከትል ስጋት እንዳለ እየተገለጸ ነው። ትግራይ ክልልን ጨምሮ በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች የሚሰሩ ስምንት ሲቪል ማሕበራት በወቅታዊ ጉዳዮች ዙርያ ትላንት ያሰራጩት መግለጫ እንደሚለው፥ የሰላምና ውይይት ጥሪ በተደጋጋሚ ቢቀርብም እስካሁን የተገኘ ውጤት የለም ። ይልቁንም በትግራይ ያሉት ፖለቲካዊ ልዩነቶች ሰፍተዋል፣ ግጭቶች ተባብሰው፣ በአጠቃላይ አሳሳቢ ሁኔታ ተፈጥሯል ይላል መግለጫው ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ ከመቀሌ ተጨማሪ ዘገባ አለው ።
የግጭት ስጋት
ቅድሚያ ለሰብአዊ መብቶች፣ ድምፂ፣ ይኾኖ እና ጎርዞ የተባሉ የመብት ተሟጓቾች ድርጅቶች ጨምሮ ስምንቱ ሲቪል ማሕበራት፥ ጦርነት በማንኛውም ይሁን ሁኔታ መቅረት ያለበት ክስተት ነው የሚሉ ሲሆን እየታዩ ላሉ ፖለቲካ ችግሮች ፖለቲካዊ መፍትሔ ብቻ እንዲበጅላቸው ጥሪ አቅርበዋል።
መግለጫው ካወጡት መካከል የሆኑው የዴሞክራሲና ማሕበራዊ ፍትህ ድምፅ ስራ አስከያጅ አቶ መልአኩ ሃይሉ፥ ለዶቼቬለ እንዳሉት በትግራይ ሐይሎች መካከል የተፈጠረ ክፍፍል ተከትሎ የእርስበርስ ግጭት እንዳይከሰት፥ ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ በኢትዮጵያ መንግስት እና ህወሓት መካከል ያለው አለመተማመን ሌላ ዙር ጦርነት እንዳያስከትል ስጋት ተከስቶ እንዳለ ተናግረዋል።
የልሂቃን ሚና
ስምንቱ ሲቪል ማሕበራት ያለው አስጊ ሁኔታ በመረዳት ወጣቶች፣ ሚድያ ተቋማት፣ ሲቪል ማሕበራት፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሃይማኖት መሪዎች እና ሌሎች በአንድ ድምፅ ጦርነት ያውግዙ ብለዋል። የዴሞክራሲና ማሕበራዊ ፍትህ ድምፅ ስራ አስከያጅ አቶ መልአኩ ሃይሉ በተለይም ልሂቃን ገንቢ ሚና ሊጫወቱ ይገባል ብለዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ የትግራይ ግዚያዊ አስተዳደር ፕሬዝደንት ሌተናንት ጀነራል ታደሰ ወረደ በኢትዮጵያ የዓለም ስደተኞች ድርጅት ሐላፊ ከሆኑት ኣቢባትዩ ዌን ጋር መወያየታቸው የገለፀው የክልሉ ኮምኒኬሽን ፅሕፈት ቤት፥ በአስቸጋሪ ሁኔታ ላይ ተሁኖ ጭምር የጦርነት ደመና ለማራቅ እና ሰላም ዘላቂ ለማድረግ እየሰሩ እንዳለ ለሐላፊዋ መግለፃቸው አመልክቷል።
ጦርነት ማስቀረት
የኢትዮጵያ ፌደራል መንግስት ትግራይ ወደ ጦርነት ለመግባት ዝግጅት እያደረገች ነው የሚል ስጋት አለው ብለው እንደሚያስቡ ጀነራል ታደሰ የገለፁ ሲሆን፥ ይሁንና በየትኛውም ምክንያት ወደ ጦርነት ላለመመለስ ጥረቶች እየተደረጉ መሆኑ፣ በትግራይ በኩል የሚጀመር ማንኛውም ግጭት እንደማይኖርም ማረጋገጣቸውን የትግራይ ኮምኒኬሽን ፅሕፈት ቤት ያሰራጨው ፅሑፍ ያመለክታል።
ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ
ኂሩት መለሰ
ታምራት ዲንሳ























