ስለ 7ኛዉ ብሔራዊ ምርጫ ቀን እና ተያያዥ ጉዳዮች ምን ያህል ሕዝብ ያውቃል
Description
የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ የ 7ኛውን ሀገራዊ ጠቅላላ ምርጫ የጊዜ ሰሌዳ ከሁለት ሳምንት በፊት ለሕዝቡ ይፋ ማድረጉ ይታወቃል። ቦርዱ በይፋ ባወጣው በዚህ የጊዜ ሰሌዳ ሀገራዊው የድምጽ መስጫ ቀን ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም መሆኑን አመልክቷል። ያም ሆኖ ዶቼቨሌ ያነጋገራቸው የአዲሰ አበባ ነዋሪዎች 164 ቀናት ብቻ የቀረው 7ኛው ብሔራዊ ምርጫ ተሳታፊ እንደሆኑ ቢናገሩም ምርጫው የሚካሄድበትን ቀን እርግጠኛ አይደሉም። ምን ያህል ተፎካካሪ ፓርቲዎች ለምርጫ እንደቀረቡም በቂ መረጃ የላቸውም ።
ቦርዱ ባወጣው የጊዜ ሰሌዳ ሄደት መሠረት የምርጫ ጽ/ ቤት የማደራጀቱ ሥራ እስከ ታኅሣሥ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ይቀጥላል። 7ኛው ዙር ጠቅላላ ምርጫ በሁሉም ክልል እና ከተማ አስተዳድር የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና የክልል ምክር ቤት ቤት አባልት ብዛትን በዝርዝር አስቀምጧል።
ስባተኛው ሀገራዊ ምርጫ ዘንድሮ በተለየ መልኩ ለመራጮች የዲጂታል ምዝገባ ማካሄድ እንደሚጀምርም ካውጣው የጊዜ ሰሌዳ መረዳት ይቻላል። ይኸውም መራጮች በቴክኖሎጂ ታግዘው ባሉብት ሆነው መመዝገብ የሚችሉበት ነው። ይህ እራስን ለመራጭነት ለማዘጋጀት የሚደረገው ምዝገባ እንደ ምርጫ ቦርድ የሥራ ዝርዝር ከሆነ ከያዝነው ወር መጨረሻ ይጀምራል፤ ታኅሣሥ 30 ቀን 2018 ዓ.ም። ያም ሆኖ ይህንን ዘንድሮ የሚካሄደውን ምርጫ በተመለከተ ዶቼ ቪሌ ያነጋገራቸው የአዲስ አበባ ነዋሪዎች፤ ምርጫ መኖሩን እንጂ ቀኑ መቼ እንደሆን አናውቅም ሲሉ ተናግረዋል።
የ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባለፉት ቀናት የፖለቲካ ፓርቲዎች ዕጩዎች ምዘገባ ቀነ ገደብን እንደሚያራዝም ባወጣው መግለጫ አስታውቋል። ምን ያህል ተፎካካሪ ፓርቲ አንዳለ ያውቁ እንደሆነ ያንጋገርኩዋቸው እነዚሁ ሰዎች የተለያዩ ሃሳቦችን ሰንዝረዋል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በ7ተኛው ጠቅላላ ምርጫ የሚወዳደሩ የፖለቲካ ፓርቲዎች የምረጡኝ ቅስቀሳ ከጥር 1 እስከ ግንቦት 19 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚካሄድ የምርጫ ቦርድ ያወጣው የጊዜ ሰሌዳ ያሳያል።
ሃና ደምሴ
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ























