እናት ፓርቲ ከቅንጅት ተሰረዝኩ ሲል ብሔራዊ ምርጫ ቦርድን ወቀሰ
Description
እናት ፓርቲ «ከቅንጅት ተሳትፎ በማግለል የእናት ፓርቲን እንቅስቃሴ መገደብ አይቻልም» ሲል መግለጫ አወጣ። ፓርቲዉ ትናንት ይህን መግለጫ ያወጣዉ፤ ምርጫ ቦርድ የ5 ፓርቲዎች ስብስብ ሆኖ ከተመሰረተዉ ከ«ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት» ቅንጅት ዉስጥ ሰርዞኛል ሲል ነው። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድን ለማነጋገር ያደረግነዉ ጥረት ለዛሬ አልተሳካም።
እናት ፓርቲ በቅንጅት ሲንቀሳቀስ ከነበረበት የፓርቲዎች ጥምረት በምርጫ ቦርድ መሰረዙን ገልጾ የወቀሰበትን መግለጫ ይፋ ያደረገዉ ትናንት ከቀትር በኋላ ነበር። እናት ፓርቲ ከመላዉ ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት «መኢአድ» ፤ ከኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ «ኢህአፓ» ከኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ «አዴፓ» እና ከአማራ ግዮናዊ ንቅናቄ «አግን» ጋር «ጠንካራ መሰረት» ሲል የገለፀውን መሰረት የጣለ ትብብር ፈጥሮ ሲንቀሳቀስ መቆየቱን ጠቅሷል ። ሕዝብም በጥምረቱ ደስተኛ እንደነበር የገለፁት የፓርቲዉ አመራር አቶ ጌትነት ወርቁ «አሁን ግን በምርጫ ቦርድ ተወግደናል ሲሉ» ለዶቼ ቬለ ተናግረዋል።
«ትብብሩ በወሳኝ አገራዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ አቋም በመያዝ ጠንካራ የሕዝብ ድምፅ መሆን የቻለ» መሆኑን በመጥቀስ «ይህ አቋሙና አካሄዱ ፓርቲውን እና የትብብሩን አባል ፓርቲዎችን በገዥው ፓርቲም ሆነ በመንግሥት በጠላትነት እንዲፈረጁ አድርጓል ሲል የእናት ፓርቲ መግለጫ ይጠቅሳል። የፓርቲዎቹ ትብብር ሕጋዊ መልክ ይዞ በአዋጅ በተደነገገው መሠረት ወደ ቅንጅት እንዲያድግ እናት ፓርቲ «ከሌሎች የትብብሩ አባል ፓርቲዎች ጋር ከፍ ያለ ጥረት በማድረግ መስከረም 10 ቀን፣ 2018 ዓ.ም ሦስት የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ተወካዮች በተገኙበት ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት በይፋ» መመስረቱን የእናት ፓርቲ አመራር ገልፀዋል። ፓርቲያቸዉ እንቅስቃሴዉን እንደሚቀጥልም ተናግረዋል።
እናት ፓርቲ ሌሎች አራት ፖለቲካፓርቲዎች የተጣመረበት የ5 ፓርቲዎች ስብስብ «ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት» የተሰኘው ቅንጅት ከመጭው ምርጫ በፊት የኢትዮጵያ መንግስት በሀገሪቱ ሰላም እንዲያሰፍን በሳምንቱ መጀመርያ ሰኞ መግለጫ ማዉጣቱን መዘገባችን ይታወቃል። እናት ፓርቲ ከቅንጅት ተሳትፎ በምርጫ ቦርድ ተሰርዝኩ ሲል ያወጣዉን መግለጫ ይዘን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድን ለማነጋገር ያደረግነዉ ተደጋጋሚ ጥረት ለዛሬ አልተሳካም። ጥረታችንን እንቀጥላለን።
አዜብ ታደሰ
ማንተጋፍቶት ስለሺ























