DiscoverDW | Amharic - Newsየሚያዝያ 20 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ
የሚያዝያ  20 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የሚያዝያ 20 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

Update: 2025-04-28
Share

Description

ሊቨርፑል የፕሬሚየር ሊጉን ዋንጫ መውሰዱን ገና አራት ጨዋታዎች እየቀሩት አረጋግጧል ። በላሊጋው በቀዳሚነት የሚገሰግሰው ባርሴሎና ደግሞ የኮፓ ዴል ሬይ ዋንጫን ከሪያል ማድሪድ ጋር አንገት ለአንገት ተናንቆ መንትፏል ። በዓለም አትሌቲክስ የፕላቲንየም ደረጃ በተሰጠው የለንደን ማራቶን የሩጫ ፉክክር ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ትእግስት አሰፋ ክብረ-ወሰን በመስበር ጭምር አሸናፊ ሁናለች ። የፓሪስ ኦሎምፒክ የማራቶን ባለድሉ ኢትዮጵያዊው አትሌት ታምራት ቶላ በተሳተፈበት የወንዶች ፉክክር ግን ድሉ የኬንያውያን አትሌቶች ሁኗል ። ተጨማሪ ዘገባዎችንም አካተናል፥



አትሌቲክስ



ለንደን ውስጥ እሁድ የሚያዝያ 19 ቀን፣ 2017 ዓ.ም በተከናወነው በለንደን ማራቶን ሩጫ ፉክክር ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ትእግስት አሰፋ የዓለም ክብረወሰንን ጭምር በማሻሻል አሸንፋለች ። ትእግስት አሸናፊ የሆነችው የበቃችው ርቀቱን 2 ሰዓት ከ15 ደቂቃ ከ50 ሰከንድ ሮጣ በመግባት ነው ። የሴቶች ማራቶን የምንጊዜም ክብረ-ወሰን ተይዞ የቆየው በኬንያዊቷ ሯጭ ሩትዝ ቼፕንጊትች ነበር ።



ሩትዝ ባለፈው ዓመት የቺካጎ ማራቶን ውድድርን ያጠናቀቀችው 2 ሰዓት ከ9 ደቂቃ ከ56 ሰከንድ በመሮጥ ነበር፥ ከትናንቱ የትእግስት ሰአት ልዩነቱ የስድስት ሰከንድ ነው ። የባለፈው ዓመት የለንደን ማራቶን ባለድል ደግሞ ኬንያዊቷ ፔሬስ ጂፕቺርቺር ነበረች ። ፔሬስ 2 ሰዓት ከ16 ደቂቃ ከ16 ሰከንዶች በመሮጥ የሴቶች ብቻ የዓለም ክብረ ወሰንን ባስመዘገበችበት ወቅት ትዕግሥት አሰፋ ሁለተኛ ደረጃ አግኝታ ነበር ። ትናንት ደግሞ የለንደን ብቻ ሳይሆን የሴቶች የምንጊዜም ክብረወሰንን ሰብራለች ።



የሁለተኛ ደረጃውን ከትእግስት በሁለት ደቂቃ ከ54 ሰከንድ ተቀድማ ያገኘችው ኬንያዊቷ አትሌት ጆይሲሊን ጄፕኮስጊ ናት ። በትናንቱ የለንደን ማራቶን ውድድር ታሸንፋለች በሚል ቅድመ-ግምት ተሰጥቷት የነበረችው ትውልደ ኢትዮጵያ ኔዘርላንዳዊቷ አትሌት ሲፈን ሐሰን ከትእግስት ሦስት ደቂቃ ከዐሥር ሰከንዶች ዘግይታ በመግባት (በ2 ሰዓት ከ19 ደቂቃ) ሦስተኛ ደረጃ አግኝታለች ። ኢትዮጵያዊቷ ሄቨን ኃይሉ አራተኛ ወጥታለች።



በዓለም አትሌቲክስ የፕላቲንየም ደረጃ በተሰጠው የወንዶች ለንደን ማራቶን ፉክክር ግን ኬንያዊው አትሌት ሰባስቲያን ኪማሩ ሳዌ ርቀቱን 2 ሰአት ከ2 ደቂቃ ከ27 ሰከንድ በማጠናቀቅ ለድል በቅቷል ። ኡጋንዳዊው አትሌት ጄኮብ ኪፕሊሞ ከሰባስቲያን በአንድ ደቂቃ ከዐሥር ሰከንድ ተበልጦ የሁለተኛ ደረጃ አግኝቷል ። ሌላኛው ኬኒያዊ አትሌት አሌክሳንደር ሙንያዎ የአገሩ ልጅን በአንድ ደቂቃ ከ53 ሰከንድ ተከትሎ በሦስተኛነት አጠናቋል ። ትውልደ ሶማሊያው ኔዘርላንዳዊ ሯጭ አብዲ ናጊዬ ከአሌክሳንደር እኩል ሰአት ገብቶ የአራተኛ ደረጃ አግኝቷል ። የፓሪስ ኦሎምፒክ የማራቶን ባለድሉ አትሌት ታምራት ቶላ 2 ሰአት ከ4 ደቂቃ ከ42 ሰከንድ በመግባት አምስተኛ ደረጃ በመያዝ ውድድሩን አጠናቀዋል ። ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት ሚልኬሳ መንገሻ በዐሥረኛ ደረጃ (2:09:01 )አጠናቅቋል ።



እግር ኳስ



በጀርመን ቡንደስሊጋ ትናንት ቦሁም ከዑኒዮን ቤርሊን ጋር አንድ እኩል ቬርደር ብሬመን ከሳንክት ፓውሊ ጋር ያለምንም ግብ ተለያይተዋል ። ቅዳሜ ዕለት በነበሩ ግጥሚያዎች፦ አይንትራኅት ፍራንክፉርት ላይፕትሲሽን 4 ለ0 ጉድ አድርጓል ። ቮልፍስቡርግ በፍራይቡርግ የ1 ለ0 ሽንፈት አስተናግዷል ። መሪው ባዬርን ሙይንሽን ሜዳው አሊያንትስ አሬና ውስጥ ማይንትስን 3 ለ0 ድል አድርጓል ። ቦሩስያ ዶርትሙንድ ሆፈንሀይምን 3 ለ2 ሲያሸንፍ፤ ቦሩስያ ሞይንሽንግላድባኅ ወራጅ ቀጣናው ውስጥ በ17ኛ ደረጃ በሚዳክረው ሆልሽታይን ኪዬል የ4 ለ3 ያልተጠበቀ ሽንፈት ገጥሞታል ። ከባዬርን ሙይንሽን በስምንት ነጥብ ተበልጦ በ67 ነጥቡ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ባዬር ሌቨርኩሰን አውግስቡርግን 2 ለ0 ድል አድርጓል ።



የእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ



የእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ገና ሳይጠናቀቅ ሊቨርፑል የዋንጫ ባለድል መሆኑን ከወዲሁ አረጋግጧል ። የሊቨርፑል አሰልጣኝ አርኔ ስሎት በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ አሰልጣኝነት አዲስ ታሪክ አስመዘገቡ ። ምንም እንኳን ኔዘርላንዳውያን አሰልጣኞች በአውሮጳ ሊጎች ስኬታማ ቢሆኑም፦ የሊቨርፑል አሰልጣኝ አርኔ ስሎት ግን በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ታሪክ ቡድናቸውን ለዋንጫ ድል በማብቃት የመጀመሪያው ኔዘርላንዳዊ ሆነዋል ። የሚያዝያ 13 ቀን 2017 ዓ.ም፤ የስፖርት ዝግጅት



የ46 ዓመቱ አሰልጣኝ፦ ሊቨርፑል በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ከአራት ዙር ጨዋታዎች አስቀድሞ ዋንጫውን ማንሳቱን እንዲያረጋግጥ አስችለዋል ። በእርግጥም ከጀርመናዊው አሰልጣኝ ዬርገን ክሎፕ አንድን ቡድን መረከብ ሁልጊዜም እጅግ ፈታኝ ነው ። ሆኖም ኔዘርላንዳዊው አሰልጣኝ እንደውም የተሻሉ ተተኪ አሰልጣኝ መሆናቸውን አስመስክረዋል ። በዚህ ድላቸውም ከኔዘርላንድ ውጪ ያሰለጠኗቸው ቡድኖቻቸው ዋንጫ እንዲያገኙ ማብቃት ከቻሉ አሰልጣኞች ተርታ ተሰልፈዋል ።



አሰልጣኝ ሪኑስ ሚሼልስ፣ ዮሐን ክሩይፍ፣ ሌዎ ቤንሐከር፣ ሉዊ ቫን ጋል እና ፍራንክ ሪክያርድ ከኔዘርላንድ ውጪ ቡድኖቻቸው ለዋንጫ ድል ያበቁ አሰልጣኞች ናቸው ። አሰልጣኝ ዮሐን ክሩይፍ እና ፍራንክ ሪክያርድ የስፔን ሊግ ዋንጫ አሸናፊዎች ነበሩ ። ከሁለት ሳምንት በፊት ሰኞ በ82 ዓመታቸው ያረፉት ሌዎ ቤንሐከር ደግሞ በላሊጋው የሪያል ማድሪድ አሰልጣኝ ሁነው ቡድናቸውን ለዋንጫ ማብቃት ችለዋል ።



ሌላኛው አሰልጣኝ ሉዊ ቫን ጋል በስፔን ላሊጋ ባርሴሎናን እንዲሁም በጀርመን ቡንደስሊጋ ባዬርን ሙይንሽንን ለድል በማብቃት ስማቸው የገነነ ነው ። ሆኖም ከእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ የማንቸስተር ዩናይትድ የሁለት የጨዋታ ዘመን ቆይታቸው የተሰናበቱት ገናና ስማቸው ጠልሽቶ ነው ። ልክ እንደ ሉዊ ቫን ጋል ሁሉ ሌላኛው የኔዘርላንድ አሰልጣኝ ሩድ ቫን ኒስተርሎይ በፕሬሚየር ሊጉ ስኬት ርቋቸዋል ። ያም ብቻ አይደለም ባለፉት 12 ግጥሚያዎቹ በዐሥራ አንዱም ማሸነፍ የተሳነው ቡድናቸው ላይሰር ሲቲ ወራጅ ቃጣናው ውስጥ እጣ ፈንታውን ይጠባበቃል ።



የኔዘርላንዳዊው የሊቨርፑል አሰልጣኝ አርኔ ስሎት ስኬት



በነገራችን ላይ እነ ፍራንክ ደ ቦይር፣ ሩድ ጉሊት፣ ጉስ ሒድኒክ፣ ዲክ አድቮካት እና ሮናልድ ኮይማን በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ አሰልጣኝነት ተፈትነው የወደቁ የኔዘርላንድ አሰልጣኞች ናቸው ። ከነዚህ ሁሉ ኔዘርላንዳውያን አሰልጣኞች መካከል ግን አንዱ ጎልማሳ ተሳክቶላቸዋል ። አሰልጣኝ አርኔ ስሎት ። በቀያዮቹ ደጋፊዎቹ ጢም ብሎ በሞላው አንፊልድ ስታዲየሙ ውስጥ ሊቨርፑል ቶትንሀም ሆትስፐርን 5 ለ1 ሲያደባይ ዋናው ሰው ኔዘርላንዳዊው አሰልጣኝ አርኔ ስሎት ነበሩ ። ሊቨርፑል የትናንት ድሉ 20ኛ የዋንጫ ድሉ ሁኖ ተመዝግቦለታል ።



አምስቱን ግቦች ሉዊስ ዲያዝ፣ አሌክሲስ ማክ አሊስተር፣ ኮዲ ጋክፖ እና የግብ ቀበኛው መሐመድ ሣላኅ ከመረብ አሳርፈዋል ። የሊቨርፑልን ብርቱ የማጥቃት ጫና መቋቋም የተሳነው ቶትንሀም ሆትስፐር በግራ ተመላላሹ ዴስቲኒ ኡዶጂ ስህተት አምስተኛ ግብ በገዛ መረቡ ላይ ተቆጥሮበታል ። ብቸናዋን የማጽናኚያ እና ቀዳሚ ግብ በ12ኛው ደቂቃ ላይ ያስቆጠረው ዶሚኒክ ሶላንኬ ነው ።



ሆኖም ሊዊስ ዲያዝ ብዙም ሳይቆይ በአራት ደቂቃ ውስጥ ሊቨርፑልን አቻ ካደረገ በኋላ ቶትንሀም ሆትስፐር የቀያዮቹን ውርጅቢኝ መቋቋም ተስኖት 5 ለ1 ተፍረክርኳል ። በዚህም ሊቨርፑል ከእንግዲህ ማንም ሊደርስበት የማይችለውን 82 ነጥብ በመሰብሰብ ዋንጫውን ከወዲሁ መውሰዱን አረጋግጧል ። ያም ብቻ አይደለም ። ግብጻዊው ግብ አዳኝ ሞሐመድ ሳላኅ በ28 ከመረብ ያረፉ ኳሶቹ በኮከብ ግብ አግቢነት የሚደርስበት አልተገኘም ። የኒውካስሉ አሌክሳንደር ኢሳቅ በ22 እንዲሁም የማንቸስተር ሲቲው ኧርሊንግ ኦላንድ በ21 ሞሐመድ ሣላኅን ይከተሉታል ።



ሊቨርፑል በቀጣይ አራት ጨዋታዎች ከቸልሲ፣ ከአርሰናል፣ ከብራይተን እና ክሪስታል ፓላስ ጋር ይጋጠማል ። ጨዋታዎቹ ዋንጫ መውሰዱን ላረጋገጠው ሊቨርፑል የሚቀይረው ነገር የለም ። ለብዙዎቹ ግን እጅግ ወሳኝ ግጥሚያ ነው ። የሚያዝያ 6 ቀን 2017 ዓ.ም. የስፖርት ዝግጅት



አምስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ቸልሲ በቀጣ የሻፕሚዮንስ ሊግ ተሳታፊ ከሚሆኑ አምስት የፕሬሚየር ሊግ ቡድኖች መካከል ላለመውጣት ከሊቨርፑል ጋር የሞት ሽረት ግጥሚያ ማድረጉ የማይቀር ነው ። ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው አርሰናል 67 ነጥብ ቢኖረውም ስድስተኛ ደረጃ ላይ ያለው ኖቲንግሀም ፎረስት እንደ ቸልሲ 60 ነጥብ አለው ። 7ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው አስቶን ቪላም በ57 ነጥቡ ወደ ሻምፒዮንስ ሊግ የመግባት እድሉ ገና አልተጨናገፈም ። አርሰናል በቀጣይ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳታፊ ለመሆን ሁለት ጨዋታዎችን የግድ ማሸነፍ ይጠበቅበታል ። ስለዚህ ከሊቨርፑል ጋር የሚያደርገው ጨዋታው ለአርሰናል የሞት ሽረት ነው ።



እንደ ፉልሀም ሁሉ 51 ነጥብ ያለው ብራይተንም ቢሆን በሻምፒዮንስ ሊግ አለያም በአውሮጳ ሊግ ተሳታፊ ለመሆን አራቱንም ግጥሚያዎቹን አሸንፎ የሌሎቹን መሸነፍ ይጠብቃል ። 45 ነጥብ ሰብስቦ 12ኛ ደረጃ ላይ ለሚገኘው ክሪስታል ፓላስ ግን ከሊቨርፑልም ጋር ሆነ ከሌሎች ቡድኖች ጋር የሚያደርጋቸው ጨዋታዎችን አሸነፈም ተሸነፈም የሚፈይድለት ነገር አይኖርም ።



ባርሴሎና የኮፓ ዴል ሬይ ዋንጫ ባለድል



እጅግ ድንቅ በሆነ ቀዳሚ ግብ ጀርመናዊው አሰልጣኝ ዲተር ሐንሲ ፍሊክ ሪያል ማድሪድን በማሸነፍ በስፔን የኮፓ ዴል ሬይ ዋንጫ ድልን ከባርሴሎና ጋር ተቀዳጁ ። ለባርሴሎና ቀዳሚዋን ግብ በ28ኛ ደቂቃ ላይ ከርቀት አክርሮ በመምታት በድንቅ ሁኔታ ከመረብ ያሳረፈው ፔድሪ ነው ። ኳሷን ሰባት ተጨዋቾች ለመከላከል ከተደረደሩበት መሀል አሳልፎ ለፔድሪ ያቀበለው ላሚና ያማል ብቃቱን ዐሳይቶበታል ። ከረፍት መልስ በ70ኛ ደቂቃ ኬሊያን እምባፔ አቻ የምታደርገውን ግብ እስካስቆጠረ ድረስ ሪያል ማድሪድ አንድ ለዜሮ እየተመራ ነበር ። ኬሊያን እምባፔ ፍጹም ቅጣት ምት ክልል አቅራቢያ ተጠልፎ የተገኘውን ቅጣት ምት ራሱ መትቶ ግሩም በሆነ ሁኔታ ከመረብ አሳርፏል ። የባርሴሎናን አሸናፊነት መንፈስ ላይ ውኃ የቸለሰ አጋጣሚ፥ የሪያል ማድሪዶችን ያነቃቃ አጋጣሚ ።



አፍታም ሳይቆይ በ77ኛው ደቂቃ ላይ አውሬሊየን ቾውሚኒ ሁለተኛውን ግብ አስቆጥሮ ድሉ የሪያል ማድሪድ መሰለ ። አሰልጣኝ ካርሎ አንቼሎቲ ኬሊያን እምባፔን ከተቀያሪ ወንበር ወደ ሜዳ ማስገባታቸው በእርግጥም ፍሬ ማፍራቱን ዐሳይቷል ። ቢያንስ መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሊጠናቀቅ ስድስት ደቂቃ እስኪቀረው ድረስ ። የመጋቢት 29 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ



84ኛው ደቂቃ ላይ የባርሴሎናን ተስፋ ያንሰራራ ግብ በፌራን ቶሬስ ተቆጠረ ። ኳሷን እንደተለመደው ዙሪያውን ከከበቡት ተጨዋቾች መሐከል አሾልኮ ለፌራን ያቀበለው ላሚና ያማል ነው ። ፌራን ቶሬዝ ተከላካዩ ሩዲገር እና ግብ ጠባቂው ቲቦ ኮቱዋን አታሎ ኳሷን ከመረብ አሳርፏል ። መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ተጠናቆ በጭማሪውም ሁለቱ ኃያላን ቡድኖች ሁለት እኩል እንደሆኑ ዘለቁ ። አሁን ጨዋታው በአቻ ተጠናቅቆ ወደ መለያ ምት ማምራቱ አይቀርም የሚለው የብዙዎች ግምት ሆነ ።



የሁለቱም ቡድን ተጨዋቾች ተዳክመዋል ። ምናልባትም የመለያ ምቱ ቶሎ በደረሰ ይሉም ይሆናል ። ሁሉም ነገር ሊጠናቀቅ አራት ደቂቃ ሲቀረው ግን ያልታሰበ ነገር ተከሰተ ። ጁሌስ ኩንዴ በሴቪያ ሰማይ እኩለ ሌሊት የባርሴሎና ደጋፊዎችን ያስፈነጠዘውን ግብ አስቆጠረ ። ርችቱ ተንቦገቦገ ። ተጨዋቾቹ ጁሌስ ኩንዴን ለማቀፍ ሜዳውን ወረሩት ። ስታዲየሙ በደስታ ተደበላለቀ ። በዚያ ግን አላበቃም ።



ጨዋታው ሊጠናቀቅ ሲል ኬሊያን ምባፔ ፍጹም ቅጣት ምት ክልል ውስጥ ወደቀ ። የመሐል ዳኛው ጣታቸውን ለፍጹም ቅጣት ምት ሲያመለክቱ የመሥመር ዳኛው ግን ባንዲራቸውን ከፍ አድርገው ነበር፤ ከጨዋታ ውጪ ምልክት ለማሳየት ። ፍጹም ቅጣት ምቱም ሳይሰጥ የመሐል ዳኛው ፊሽካቸውን ነፉ፥ ጨዋታ ተጠናቀቀ ።



ሪያል ማድሪዶች አበዱ ። በተለይ ወደ መጨረሻ አካባቢ ተቀይሮ የወጣው አንቶኒዮ ሩዲገር ንዴቱን መቆጣጠር አቅቶት ለተጎሻሸመ ሰውነቱ የተሰጠውን በላስቲክ የተከማቸ በረዶ ወደ ዳኛው በተነ ። እናም በተፈጠረው ትርምስ ሦስት የሪያል ማድሪድ ተጨዋቾች ቀይ ካርድ ተሰጣቸው ። የስፔኑ ተከላካይ ሉቃስ ቫስኩዌዝ፣ የጀርመን ብሔራዊ ቡድን ተከላካዩ አንቶኒዮ ሩዲገር እና የእንግሊዙ አማካይ ጁድ ቤሊንግሀም ። ምናልባትም አንቶኒዮ ሩዲገር ባሳየው ጠባይ ከበድ ያለ ቅጣትም ሊጠብቀው ይችላል ።



በላሊጋውም ባርሴሎና ከሪያል ማድሪድ በአራት ነጥብ ርቆ በ76 ነጥብ ይመራል ። ከቀሪ አምስት ጨዋታዎቹ በሁለተኛው የፊታችን እሁድ ሳምንት ባርሴሎና ከሪያል ማድሪድ ጋር ዳግም ይገናኛል ። ሪያል ማድሪድ የኮፓ ዴል ሬይ ሽንፈቱን ለመበቀል ብቻ ሳይሆን የላሊጋውን ዋንጫ ላለማጣት በባርሴሎና ላይ የተሳሉ ጥርሶቹን ይበልጥ ሞርዶ ነው ወደ ሜዳ የሚገባው ። የኮፓ ዴል ሬይ አሸናፊው ማለትም ባርሴሎና እና ተከታዩ ሪያል ማድሪድ፤ እንዲሁም ከላሊጋው የዋንጫ አሸናፊ እና ሁለተኛ የሚወጣው ቡድን በስፔን ሱፐር ካፕ ዋንጫ ግጥሚያ ይፋለማሉ ። ያው እኒሁ ባርሴሎና እና ሪያል ማድሪድ መሆናቸው ነው ።



በነገራችን ላይ በሴቶች እግር ኳስ ግጥሚያም ባርሴሎና ቸልሲን 4 ለ1 በድምሩ 7 ለ1 ድል አድርጎ ለዋንጫ ፍጻሜ አልፏል ። በደርሶ መልስ ኦሎምፒክ ሊዮንን ስድስት ለአንድ ረትቶ ለፍጻሜ ከደረሰው የእንግሊዙ አርሰናል ጋር ባርሴሎና ከሦስት ሳምንት በኋላ ለዋንጫ ይፋለማል ። ባርሴሎና ዳግም በሴቶቹም ይቀናው ይሆን?



ማንተጋፍቶት ስለሺ



ፀሐይ ጫኔ

Comments 
In Channel
loading
00:00
00:00
x

0.5x

0.8x

1.0x

1.25x

1.5x

2.0x

3.0x

Sleep Timer

Off

End of Episode

5 Minutes

10 Minutes

15 Minutes

30 Minutes

45 Minutes

60 Minutes

120 Minutes

የሚያዝያ  20 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የሚያዝያ 20 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ማንተጋፍቶት ስለሺ ሥዩም Mantegaftot Sileshi