ፈረንሳይ ውስጥ የበርካቶችን ሕይወት የቀጠፈው የሽብር ጥቃት 10ኛ ዓመት
Description
ከአስር ዓመታት በፊት በዛሬው ቀን በተለያዩ የፓሪስ ምግብ እና ቡና ቤቶች፤ እንዲሁም በፈረንሳይ ስታድየም አቅራቢያ በርካታ ጥቃቶች ተፈጽመው ሕይወት ቀጥፈዋል። በዕለቱ ጥቃቱ ሲደርስ በርካታ እግር ኳስ አፍቃሪዎች በስታዲየሙ የፈረንሳይ እና ጀርመን ብሔራዊ ቡድኖችን ጨዋታ እየተመለከቱ ነበር። በተመሳሳይ የአሜሪካው ኤግልስ ኦፍ ዴዝ ሜታል የተሰኘው ባንድ ፓሪስ ውስጥ የሙዚቃ ድግሱን በሚያቀርብበት አዳራሽ ውስጥም የተፈጸመው ጥቃት የ90 ሰዎችን ሕይወት መንጠቁ ለታሪክ ተመዝግቧል። ጥቃት በተፈጸመባቸው በሁሉም ስፍራዎች ከሞቱት በተጨማሪ በርካቶች ተጎድተዋል።
ፈረንሳይ ይህን ጥቃት በተለያዩ ዝግጅቶች አስባ የዋለች ሲሆን፤ ፕሬዝደንት ኢማኑዌል ማክሮ በፓሪስ ስታዲየም ፊትለፊት በመገኘት አበባ አስቀምጠዋል። በጥቃቱ ሕይወታቸውን ያጡት ወገኖች ቤተሰቦች ድርጊቱ በተፈጸመባቸው ቦታዎች ተገኝተዋል። በወቅቱ ለተፈጸመው ጥቃት እራሱን እስላማዊ መንግሥት የሚለው ቡድን ኃላፊነት መውሰዱ ተገልጿል። ጥቃቱን በተግባር ከፈጸሙት 10 ሰዎች ከሚገኙበት ሴል አንዱ በሕይወት ተርፎ ተይዞ በእስር ላይ እንደሚገኝ ነው የተነገረው። የዕድሜ ልክ እስራት ፍርደኛ ነው።
ዘጠኙ አንድም እራሳቸው በአጥፍቶ ጠፊነት አልፈዋል፤ አንድም በፖሊስ ተገድለዋል። የተረፈው የ36 ዓመቱ ሳልህ አብዲሰላም ደግሞ የዕድሜ ልክ እስራት ተፈርቦበታል። የወቅቱ ፕሬዝደንት ፍራንሲስ ሆላንዴ ሀገራቸው ያለፉትን ዓመታት አንድነቷን አጠናክራ የገጠማትን ሁሉ መቋቋም ችላለች ማለታቸው ተዘግቧል። ጥቃቱ በተፈጸመበት ዕለት እግር ኳስ ለመመልከት በስታዲዮም ተገኝተው የነበሩት የቀድሞው ፕሬዝደንት ሁኔታውን አሰቃቂ በማለት ነበር የገለጹት።የጥቃቱ ሰለባዎች ቤተሰቦች የመታሰቢያ ቤተመዘክር እየተዘጋጀ ሲሆንበጎርጎሪዮሳዊው 2029 ዓ,ም ተጠናቆ ይከፈታል ተብሎ ይጠበቃል። በውስጡም 500 የሚሆኑ ከጥቃቱ ወይም ከሰለባዎች ጋር ግንኙነት ያላቸው ነገሮች ይቀመጡበታል ተብሏል። የፈረንሳዩን የሽብር ጥቃት አስረኛ ዓመት በሚመለከት የፓሪስ ዘጋቢያችን ሃይማኖት ጥሩነህን ስቱዲዮ አነጋግሬያታለሁ።
ሃይማኖት ጥሩነህ
ሸዋዬ ለገሠ
ታምራት ዲንሳ























