በትግራይ ተጨማሪ ጥቃቶችን ለመከላከል መንግስታት እርምጃ እንዲወዱ ሂውማን ራይትስ ወች አሳሰበ
Description
በሰሜን ኢትዮጵያ ፤ትግራይ ክልል ተጨማሪ ጥቃቶችን ለመከላከል ጉዳዩ ያሳሰባቸው መንግስታት እርምጃ መውሰድ አለባቸው ሲል ዓለም አቀፉ የመብት ተሟጋች ድርጅት ሂውማን ራይትስ ወች ገለፀ።
የማንቂያ ደውሎች በኢትዮጵያ ያቃጭላሉ በሚል ድርጅቱ ትናንት ህዳር 12 ቀን 2018 ባወጣው ዘገባ ፤በሰሜን ኢትዮጵያ የሚኖሩ ሰላማዊ ዜጎችን ከጦር ወንጀሎች እና ሌሎች በደሎች የሚከላከለው እርቅ አፈፃጸም ደካማ መሆኑ እና ብዙ ሀገራት ትኩረታቸው ሌላ ቦታ በመሆኑ ፣ በትግራይ ክልል እንደገና ሊስፋፋ የሚችለውን ጥቃትለመከላከል ተፅዕኖ ፈጣሪ መንግሥታት በፍጥነት መንቀሳቀስ እንደሚኖርባቸው አመልክቷል።
ድርጅቱ ለዚህ ስጋቱ መነሻ ያለው ባለፉት ሳምንታት በኢትዮጵያ መንግሥት እና በህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ ህወሓት መካከል ውጥረቱ እየጨመረ መምጣቱ ነው።በተጨማሪም በኢትዮጵያ እና በጎረቤት ኤርትራ መካከል ከፍተኛ ውጥረት እንዳለ ገልጿል። ድርጅቱ አያይዞም ዲፕሎማቶች እና ተንታኞች በሁለቱ ሀገራት መካከል የሚታዩ ቅስቀሳዎች ካለፉት ጦርነቶች የማገገም እድል ባላገኙ አካባቢዎች ዳግም ወደ ግጭት ሊያመራ እንደሚችል ለወራት ሲያስጠነቅቁ መቆየታቸውን አመልክቷል።
ከጎርጎሪያኑ 2020 እስከ 2022 በሰሜን ኢትዮጵያ የተከሰተው ግጭት ከትግራይ ተነስቶ ወደ አፋር እና አማራ ክልሎች ተስፋፍቶ እንደነበር የገለፀው ሂውማን ራይትስ ወች ጦርነቱ በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎችን ህይወት ቀጥፏል፣ ሚሊዮኖችን አፈናቅሏል፣ ወሳኝ መሠረተ ልማቶችን አውድሟል ሲልም ድርጅቱ አስታውሷል።
በጎርጎሪያኑ ህዳር 2022 የኢትዮጵያ ባለስልጣናት እና ህወሓት በአፍሪካ ህብረት አደራዳሪነት ስምምነት ተፈራርመዋል ያለው የድርጅቱ ዘገባ፤ ነገር ግን የክትትል ስልቱ በአብዛኛው ለሰብአዊ መብት ረገጣትኩረት መስጠት ባለመቻሉ የእርቁ ዋና ተዋናዮች የአፍሪካ ህብረት፣ ኬንያ፣ደቡብ አፍሪካ ፣ አሜሪካ እና የኢትዮጵያ አጋሮች ተጨማሪ የሰብአዊ መብት ረገጣን ለመከላከል በአስቸኳይ መንቀሳቀስ አለባቸው ሲል ሂውማን ራይትስ ወች አሳስቧል።
ፀሐይ ጫኔ
ልደት አበበ























