የፓርቲው የትምህርት ፖሊሲ በትምህርት ሚኒስቴር ተግባራት ውስጥ እየተፈፀመ ነው ፤ ኢዜማ
Description
የፓርቲው የትምህርት ፖሊሲ በትምህርት ሚኒስቴር ተግባራት ውስጥ እየተፈፀመ መሆኑን ኢዜማ ገለፀ
በትምህርት ሚኒስቴር ተግባራት ውስጥ የፓርቲው የትምህርት ፖሊሲ እየተፈፀመ እና ይህም "የሚኮራበት ሥራ" መሆኑን የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) ገለፀ።
ኢዜማ በመጪው 7ኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ እንደሚሳተፍ አቋሙን ለሕዝብ ይፋ ባደረገበትና የዛሬ መግለጫው ትምህርት ሚኒስቴር በሚፈጽማቸው ተግባራት "ያልተገበርነው ይኖራል እንጂ ከተተገበረው ውስጥ የኢዜማ ፖሊሲ ውስጥ የሌለ የለም" ብሏል።
የፓርቲው ብሔራዊ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል አቶ ኢዮብ መሣፍንት፤ ኢዜማ በትምህርት ሚኒስቴር ውስጥ "ለኢትዮጵያ የትምህርት ሥርዓት መፍትሔ የሚሆን" እና "መሠረት ቀያሪ" ያሉትን ሥራ መፈፀሙን እና ይህም በመጪው ምርጫ "ሕዝብን የምንቀሰቅስበት" ሥራ ነው ብለዋል።
ፓርቲው "በልዩነት ላይ የተመሠረተ፣ ብሔርን መሠረት ያደረገ ፖለቲካ እስካራመድን ድረስ ወደ ሰላም ልንሄድ አንችልም" ሲል "የዜግነት ፖለቲካን" በመከተል በምርጫው አሸናፊ ሆኖ መንግሥት ለመመሥረት እንደሚወዳደር አስታውቋል።
ለምርጫው ዝግጁ ነን
የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) ከወራት በኋላ ለሚደረገው ሀገር አቀፍ ምርጫ ለውድድር መዘጋጀቱን ይፋ ባደረገበት መግለጫው እስካሁን ከገዢው ብልጽግና ፓርቲ ጋር የተለየ ግንኙነት እንደሌለው፤ ሆኖም ከመንግሥት ጋር መሥራት "አምኖ የገባንበት" መሆኑን የፓርቲው ብሔራዊ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል አቶ ኢዮብ መሣፍንት ገልፀዋል። አክለውም ይህ ውሳኔ "ወደን ፈቅደን፣ መክረን፣ አስበንበት፣ ለሀገርም፣ ለሕዝብም፣ ለፓርቲውም ይጠቅማል ብለን የገባንበት ጉዳይ ነው" ብለዋል።
ፓርቲው በትምህርት ሚኒስቴር፣ በአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር እና በደቡብ ኢትዮጵያ ውስጥ ባሉ ክልሎች ከመንግሥት ባገኛቸው ሥልጣናት "የምንኮራበት፣ ለሕዝብ ሠርተን ማሳያየት እንደምንችል ያሳየንበት፣ የተመሰገንበት ሥራ ሠርተናል" ሲሉ በተለይም "በመንግሥት የአፈጻሚ ምክር ቤት ላይ የመቀመጥ ሥልጣን" አስገኘልን ባሉት የትምህርት ሚኒስቴርን የመምራት ዕድል የፓርቲውን የትምህርት ፖሊሲ ለማስፈጸም የቻሉበት እንደሆነ ገልፀዋል። ያም ሆኖ ግን በዚህ ሥራቸው "ውንጀላ" እንደሚቀርብባቸው አልሸሸጉም።
"በጣም የምንኮራበት ሥራ ሠርተናል። በአሁኑም ምርጫ ሕዝብን የምንቀሰቅስበት እና የምናሳየው።"
ኢዜማ ከገዢው ፓርቲ ጋር ቢሠራም የገዢው ፓርቲ ስህተት ያልናቸውን "አንድም አልፈን አናውቅም" ያሉት አቶ ኢዮብ መሣፍንት ይህን የምናደርገው "የመፍትሔ ሀሳቦችን ለማሳየት" እና ችግሩ እንዲፈታ ከመሻት መነሻ ብቻ ነው ብለዋል።
"የኢዜማን ያህል ገዢው ፓርቲ ላይ ትችት ያቀረበ ፓርቲ የለም" "ኢዜማን ስልጣን በመስጠት እና በመደለል ዝም ማስባል እንደማይቻል በበቂ አረጋግጠናል"
ለዴሞክራሲያዊ የምርጫ ፖለቲካ ያለው ምህዳር ውሱን ነው
ኢዜማ በአንዳንድ አካባቢዎች አለ ያለው "ከፍተኛ የፀጥታ ችግር" ፣ "የመንግሥት እና የገዢው ፓርቲ መቀላቀል" እና ሌሎች
ችግሮች "ለዴሞክራሲያዊ የምርጫ ፖለቲካ ያለውን ምህዳር ውሱን ማድረጉን" እንደሚረዳ፣ ሆኖም ይህን ተቋቁመን "በምርጫው እንሳተፋለን" ሲሉ የፓርቲው ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ኢዮኤል ሰለሞን በንባብ ባቀረቡት መግለጫ አረጋግጠዋል።
"በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የተከሰቱ ጦርነቶች የብሔር ፖለቲካ ውጤቶች ናቸው"
"በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የተከሰቱ ጦርነቶች የብሔር ፖለቲካ ውጤቶች ናቸው" ያሉት የኢዜማ ሊቀ መንበር ዶ/ር ሙሉዓለም ተገኘወርቅ በፊናቸው "አሁን በተግባር ሚሊዮኖችን ገብረን [ለሞት ተዳርገው] የዘር ፖለቲካ ለዚህ ሀገር እንዳማይበጅ በተግባር አይተነዋል" ሲሉ ይህም "የዜግነት ፖለቲካ" ያራምዳል ላሉት ፓርቲያቸው የማሸነፊያ ዕድል መሆኑን ጠቁመዋል።
ኢዜማ ከመንግሥት ጋር ባመሥራቱ የሚቀርብበትን ክስ አይቀበልም
ኢዜማ ከመንግሥት ጋር የመሥራቱን አሳማኝነት እንዲያስረዳ እና ከገዢው ብልጽግና ጋር በምን እንደሚለይ አሰልቺ እና ተደጋጋሚነት ያለው ጥያቄ እንደቀረበለት ገልጾ 13 ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች እና 270 ሰዎች ከመንግሥት ጋር እንደሚሠሩ በመጥቀስ ውንጀላ እንደሚበረታበት ገልጾ የሚነሳበትን ወቀሳና ትችት ውድቅ አድርጓል።
ሰለሞን ሙጬ
ታምራት ዲንሳ
ሸዋዬ ለገሰ























