አሜሪካ በኢትዮጵያ እና ኤርትራ “ግጭት እንዳይቀሰቀስ መከላከል” ላይ እንድታተኩር የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር የብሔራዊ ደሕንነት የፖሊሲ ሰነድ አሳየ
Description
ዩናይትድ ስቴትስ በኢትዮጵያ፣ ኤርትራ እና ሶማሊያ መካከል “አዲስ ግጭት እንዳይቀሰቀስ መከላከል” ላይ ማተኮር እንዳለባት የፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ይፋ ያደረገው የብሔራዊ የደሕንነት ፖሊሲ ሰነድ አሳየ።
በፕሬዝደንቱ ጽህፈት ቤት ወይም ዋይት ሐውስ በኩል ትላንት አርብ ይፋ የተደረገው የብሔራዊ የደሕንነት ስትራቴጂ ዩናይትድ ስቴትስ አፍሪካን በተመለከተ የምትከተለው አቋም መለወጥ እንደሚኖርበት ምክረ-ሐሳብ አቅርቧል።
ለረዥም ጊዜ አሜሪካ አፍሪካን በተመለከተ የተከተለችው ፖሊሲ ርዳታ እና ሊብራል ርዕዮተ-ዓለም ማስፋፋት ላይ ያተኮረ እንደነበር የተቸው ሰነድ ከእንግዲህ “ግጭትን መቀነስ” እና “የጋራ ጥቅም ያለው የንግድ ግንኙነትን ማጎልበት” ማስቀደም እንደሚኖርበት አትቷል።
ሰነዱ እንደሚለው የዩናይትድ ስቴትስ አቋም ከውጭ ርዳታ ይልቅ “የአፍሪካን የተትረፈረፈ የተፈጥሮ ሐብት እና የተደበቀ እምቅ አቅም ለመጠቀም ወደሚያስችል የመዋዕለ-ንዋይ እና የዕድገት ግንኙነት መሸጋገር” አለበት።
ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እና ሱዳንን በመሳሰሉ ሀገራት በመካሔድ ላይ ለሚገኙ ግጭቶች በድርድር መፍትሔ ማበጀት አሜሪካ ከአፍሪካ ጋር ያላትን ግንኙነት ለመለወጥ ዕድል ይሆናሉ ከተባሉ አማራጮች መካከል ይገኝበታል።
በኢትዮጵያ፣ ኤርትራ እና ሶማሊያ መካከል “አዳዲስ ግጭቶች እንዳይቀሰቀሱ” መከላከል በአሜሪካ የብሔራዊ ጸጥታ ስትራቴጂ እንደ አማራጭ የቀረበ ነው።
ዩናይትድ ስቴትስ ከአፍሪካ ጋር ከዕርዳታ ወደ ንግድ እና መዋዕለ-ንዋይ ተኮር ግንኙነት መሸጋገር እንዳለባት የሚገልጸው ሰነድ “ገበያዎቻቸውን ለአሜሪካ ዕቃዎች እና አገልግሎቶች ለመክፈት ቁርጠኛ ለሆኑ ብቁ እና አስተማማኝ ሀገራት” ቅድሚያ ሊሰጥ እንደሚገባ ምክረ-ሐሳብ አቅርቧል።
አርታዒ ዮሐንስ ገብረእግዚዓብሔር























